Translate

Tuesday, April 18, 2017

የቴዲ ‘መሠረታዊ ችግር’ ኢትዮጵያ ናት (ካሳሁን ይልማ)

ካሳሁን ይልማ
Teddy Afro New Single 2017 ‘Ethiopia’
Teddy Afro New Single 2017 ‘Ethiopia’
“ቴዲ የጎዳና ተዳዳሪ ገጭተህ ገድለሀል፣ የተገጨውንም ሰው አልረዳህም…” በሚል በቃሊቲ የታሰረበት ወቅት ነበር። የሀገሩ ርዕስ ሁሉ ቴዲ አፍሮ ነበር።
“ያቺ 17 መርፌ ናት፣… አይደለም ባክህ ሼኹ አላሙዲ ነው። ሸራተን አልዘፍንም ስላለ… ኧረ ሸራተን አይደለም.. ለሚሌኒየሙ ሼኹ ጋር እምቢ ብሎ ስታዲየምና ጅማ ስለዘፈነ ነው… ኖ ወያኔዎች እኮ በቀለኞች ናቸው። እናኳን ለቴዲ ለራሳቸውም የትግል ጓዶች የማይመለሱ አረመኔዎች…” አራት ኪሎ የነበርንበት ቦታ በክርክር ሞቅ ብሏል።እኔ እንግዳ ስለነበርኩ አስተያየት ሳልሰጥ አደምጣለሁ።
በዚህ መሐል አንድ ከፍ ያለ ድምጽ “ማን ግጭ አለው?” ሲል ተስተጋባ። ሁሉም በድንገት በመብረቅ እንደተመታ በክውታ ፀጥ ብሎ እርስ-በርስ ተያየ። እኔም ደነገጥኩ። ወዳጄ ደገመው! “ማን ገጭተህ አምልጥ አለው?!” ሲል በአለቅነትና በውስጥ-አዋቂነት ስሜት በትዕቢት ተናገረ።ታዋቂ ጋዜጠኛ እንጂ ታዋቂ ካድሬ መሆኑን አላውቅም

አላስቻለኝም። “ተው እንጂ ሲገጭ በቦታው ነበርክ ወይስ …? ለሚያልፍ ጊዜ በፈራጅነት ክፉ ባትናገር” አልኩት። ለእኔም ደገመው:: “ባይገጭ ማን ያስረዋል?”
አፌን ሲጎመዝዝኝ ተሰማኝ፣ ሬት-ሬት አለኝ። እንደዚያ በድንፋታ የሚናገረው 17 መርፌው ስለሚወጋው ነው። ከአሳሪዎቹ ወገን ስለሆነ ነው። አዲሳ’ባ ተወልዶ ካደገው ወዳጄ እንደዚህ ያለ የዘር ስሜት አይቼበት አላውቅም።
Teddy Afro (Tewodros Kassahun), the most popular artists in Ethiopia
ካሳሁን ይልማ እና ቴዲ አፍሮ
በንዴት ጦፍኹ። ብዙ እንዳልናገር የነበሩት ሌሎች ሰዎች የማላውቃቸው ስለሆኑ ክፉ-ደግ አልነጋገርም ብዬ ከቦታው ብን… ብዬ ጠፋሁ። በዚያ ምሽት የአራት ኪሎን መንገድ ብቻዬን ከራሴ ጋር እያወራሁ አዘገምኩ። በየሳምንቱ በሚያገናኘን ጉዳይ ሁለተኛ ላለመምጣት ወሰንኩ። ሰብአዊ ርኅራኄ ከሌለው ሰው ጋር ወዳጅነት ስለማያስፈልግ “ማን ግጭ አለው?” ካለው ሰው ጋር ያለኝን ቅርበት በጠስኩ።
ጊዜው ይሮጣል… 484 ቀናት። ቴዲ አፍሮ ለ16 ወራት ከታሰረበት ተለቀቀ። ባለጊዜዎቹ የጠመንጃቸውን ጉልበት ማሳየታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ፈቱት። ለማሰር ፖሊሶች፣ ለመክሰስ አቃቤ ሕግ፣ ለመፍረድ ዳኞች ናቸው። ምን ያሳናቸዋል?! አሰሩት-አሳዩት-ፈቱት።
ቴዲ በተፈታ ማግስት አዲስ ነገር ጋዜጣ ለዜና ሽፋን እኔን እና አብረሃም በጊዜውን መደበን። ከ22 ወደ ቦሌ መድኃኒ ዓለም በሚወስደው መንገድ የሚገኘው የእናቱ ራዬ (ወ/ሮ ጥላዬ) ቤት ለአዲስ ነገር ቢሮ ቅርብ ስለነበር በጠዋት ሄድን። ቅጥር ግቢውን ሰው እንደአሸን ሞልቶታል። በረንዳው ላይ እናቱ እና ሌሎች ትልልቅ ሰዎች ተደርድረዋል። የእናቱ ፊት ብሩህ ሆኗል። ውድ ልጇ ከቤቷ አለ። ፈገግታ ባጀበው ፊት ግቡ-ግቡ እያለች ዐይኗን-ብሌኗን ወደውስጥ ገብተን እንድናየው ትጋብዛለች። ቴዲ ያለው ሳሎን ክፍል ነው።
የቤቱ መተላለፊያ (corridor) በሰው ተሞልቷል።ከዚያ ሰው ሁሉ መካከል አንድ ሰው ጎልቶ ታየኝ። ነዘረኝ። “ማን ግጭ አለው?! ሲል ሲፈርድ የነበረውን ወዳጄ ለመጀመርያ ጊዜ አየሁት። ከፈረደበት ቴዲ ፈንጠር ብሎ ቁጭ ብሏል። አጠገቡ ሌላ ባለደረባው አለ። አንድ ሰው እንዴት ሁለት መሆን ይቻለዋል። አባቴ የሐረር ልጅ ነው። አዕምሮውን ይናገራል። ውስጤ የሚመላለሰውን እዚያው የፈረደበት ሰው ቴዲ ፊት፣ ወዳጆቹ ፊት ለፊት ልናገረው ፈለግሁ:: ግን ተውኩት::
የአዲስ ነገር የህትመት ቀን እንደነገ ቅዳሜ ስለነበር ወደስራችን መግባት ፈለግን። “ቃለምልልስ ልታደርጉለት ነው?” ስንል ጠየቅናቸው:: “ኧረ በፍጹም! እኛ የመጠናው እንኳን ለቤትህ አበቃህ ልንለው ነው” አለኝ ያ ቴዲ ታስሮ በነበረ ወቅት “ማን ግጭ አለው?” ሲል የነበረው ፈራጅ:: አንድ ሰው ሁለት ሰው ሆኖ አየሁ:: ሰው ሲከባችሁ፣ አጀብ ሲበዛ በፍቅር ብቻ አይደለም::
መወደዱን ስለሚጠሉ የሚጠሉት አሉ። ቴዲን ይወዱታል ግን ይጠሉታል። ቴዲን ይጠሉታል ግን ኢትዮጵያ-ኢትዮጵያ ማለቱን፣ ታሪኳን ማወደሱን ቢያቆም ከሚወዱት ይበልጥ እጅግ የሚወዱትም አሉ።  ቴዲ በበኩሉ:-
ባልፍም ኖሬ፣ 
ስለእናት ምድሬ፤
እሷ ናት ክብሬ፣ 
ኧረ እኔስ ሀገሬ::
ብሏል።
ስለዚህ ከዚህ በኋላ ይበለጥ ይጠሉታል። ችግሩ ተራራን እንደመግፋት ይሆንባቸዋል::እንዲወዱት መትጋት አያስፈልግም።ከንቱ ድካም ነው:: ምንሊክን ስላወደሰ አይደለም። በመርፌ ስለወጋ አይደለም። መሪር ጥላቻው “ኢትዮጵያ…!” ስላለ ነው። በታሪክ አለመስማማት ችግር አለው ብዬ አላምንም:: ሆኖም የቀደመ ታሪካችን ያሳረፈው ጠባሳ ላይ… ተብሎ በሚነገረውና በሚያጨቃጭቀው ብትስማማ፣ ቦምብ ዘንቦ ሕዝብ ተፈጅቷል፣ጡትም ተቆርጧል፣ ወሸላም ተሸልቷል፣ ….ወዘተ ብለህ የነገሥታትንና የታሪክን በደል አብረህ ብታስተጋባ ኢትዮጵያ ካልክ ዕጣ ፈንታው ተመስሳይ ነው። ጠላት:: ቴዲ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ የሚል ሁሉ በጥላቻ መዝገባቸው ውስጥ ይገባል። በጠላትነት ይፈረጃል። ምክንያቱም ኢትዮጵያ እየፈረሰች፣ እየተቀበረች በመቃብሯ ላይ ምናባዊ ሀገር ለመፍጠር ጉድጓድ እየተማሰ ነው።
ጉድጓዱ ጋር ላቁም::
ይቀጥላል…

No comments:

Post a Comment