Translate

Thursday, April 13, 2017

ማዕከላዊ፤ የዜጐች ዋይታ ማማ! የስቃይ ማዕከል!


  • በማዕከላዊ ስቃይ ተፀንሶ ይወለዳል፤ ጡት ጠብቶ ዳዴ ብሎ ጐልምሶ ያረጅበታል!! እንደገና አዲስ የማሰቃያ ስልት ይወለዳል!!
  • በማዕከላዊ በንጹሐን ዜጐች ደም የጨቀዩ ገራፊዎች ይርመሰመሱበታል!!
ከዝግጅት ክፍሉ፡- ማዕከላዊ አገዛዙን በወታደራዊ የበላይነትና በደህንነቱ አቅም በቁጥጥር ስሩ ያዋለው ህወሓት፤ ማዕከላዊ እስር ቤት ውስጥ እያደረሰ ያለውን ቃላት የማይገልፁት የዜጐች ስቃይ በተመለከተ ጎልጉል ድረገጽ የጥቃቱ ሰለባ የሆኑትን ዜጐችና ቤተሰቦቻቸውን በማነጋገር ይህን ዘገባ በሁለት ክፍል አጠናቅሯል። ዘገባው የጋዜጠኛነት ሙያ የሚጠይቀውን (“የሕዝብ አይንና ጆሮ በመሆን የተደበቀውን ፈልፍሎ ማውጣት!” የሚለውን) ቀዳሚ መርህ በማድረግ በዳሰሳ ጥናት ተደግፎ የተዘጋጀ መሆኑን እንገልፃለን።
የኢትዮጵያዊያን የስቃይ ጎሬ በሆነው ማዕከላዊ እስርቤት በ“ምርመራ” ወቅት በዜጎች ላይ የሚደርሱ የቶርቸር (አካላዊ ስቃይ) አይነቶች ከኢትዮጵያዊ የጋራሥነ-ልቦናና ባህል ፍፁም ያፈነገጡ ሆነው አግኝተናቸዋል። ይህም ሆኖ ለታሪክ መቀመጥ ያለበት ዘገባ በመሆኑ ከተጐጂ ዜጎችና ቤተሰቦች ያገኘነውን መረጃ ከታላቅ ጥንቃቄ ጋር አቅርበነዋል።
ክፍል አንድ
የማዕከላዊ ገጽታና የእስረኞች አያያዝ…
በአገሪቱ ርዕሰከተማ አዲስ አበባ፤ ጉለሌ ክፍለከተማ ውስጥ ይገኛል። የበርካታ ንፁሃን  ዜጎች የዋይታ ማማ፤ የስቃይ ጐሬ ነው – ማዕከላዊ እስር ቤት! ማዕከላዊ የደርግ የግፍ እጅ ሥራ ውጤት ቢሆንም ህወሓት ከደርግ በተሻለ የግፍ ድርጊት፤ ልዩልዩ የማሰቃያ ስልቶችን ተግባራዊ አድርጎበታል። ሌላው ልዩነት በደርግ ጊዜ የቶርቸር ሰለባ የነበሩት ወጣቶች ከሁሉም ቋንቋ ተናጋሪዎች የተውጣጡ የ“አብዮቱጠላቶች” ነበሩ። ዛሬ ግን ቋንቋ ተናጋሪነትንና ዘውጋዊ ማንነት ላይ ያተኮሩ የዜጐች ስቃይና ዋይታ የሚፈራረቅበት የግፍና የበቀል ማዕከል መሆኑ የህወሓቱን ማዕከላዊ ከደርጉ ማዕከላዊ ለየት ያደርገዋል። በድህረ-ደርግ በዚህ ማዕከል ውስጥ የአሰቃቂ ቶርቸር ሰለባ የሆኑ ትግራዋያንን ፈልጐ ማግኘት የሚታሰብ አይደለም። የማዕከላዊ ዋና የምርመራ ኃላፊ የሆነውን ኮማንደር ተክላይን ጨምሮ ህወሓት በከሳሽነት በሚቀርብባቸው “ፖለቲካ” ነክ ጉዳዮች ዙሪያ ዋና መርማሪ የሆኑት የትግራይ ተወላጆች ናቸው። ጥብቅ የደህንነት ፍተሻና ጥበቃ በሚደረግበት ማዕከላዊ የዋርድያ አለቆችም በተመሳሳይ ከአንድ ዘውግ የተገኙ ናቸው።
ባለፉት 26 ዓመታት ማዕከላዊ ውስጥ በተፈራራቂነት አሰቃቂ ቶርችር ከተፈፀመባቸው ወገኖች ዉስጥ፡- የኦሮሞ ወጣቶች (በኦነግ ሥም)፣ የሶማሌ ክልል በተለይም የኦጋዴን ተወላጆች (በኦብነግ ሥም)፣ የአማራ ልጆች (በተለያዩ የአማራ ድርጅቶችና ግንቦት ሰባት ስም) ቀደም ባለዉ ጊዜ ከደቡብ የሲዳማ ተወላጆች (የክልል ይገባናል መብት ጥያቄ ያነሱ) እና በቀርቡ የኮንሶ ተወላጆች (የልዩ ዞን ጥያቄ ማቅረባቸውን ተከትሎ) የመብት ጥያቄውን ያስተባበሩ የአካባቢው ተወላጆች፣… የማዕከላዊ አሰቃቂ ቶርቸር ሰለባዎች ናቸው። በዚህ የስቃይ ጐሬ ውስጥ ደራሽ ሞት በሚያስመኝ ቶርቸር የተሰቃዩት የኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት የበዛ ስቃይ ሳይጠቀስ የሚታለፍ አይደለም።
በፓርቲ ፖለቲካ ሥም በ1997ቱ በቅንጅት፣ በኋላም በአንድነት፣ በመኢአድ፣ በኦፌኮ፣ በሰማያዊ፣… ፓርቲ አባላትና የልዩ ልዩ ክልልና ዞን አመራሮች ላይ የደረሱ ዘግናኝ በደሎች የማዕከላዊ የስቃይ ታሪክ አካሎች ናቸውና የሚረሱ አይደሉም። ለሙያዊ ነፃነታቸው የታገሉ የሙያ ማህበራት አመራሮች፣ ሐሳባቸውን በነፃነት የገለፁ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞችና ጦማሪያን፣ የህወሓትን አፋኝ የአገዛዝ ፖሊሲዎች በአደባባይ የተቃወሙ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች… የስቃይ ታሪክም ከማዕከላዊ ጋር የተገናኘ ነው።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ማዕከላዊን በተመለከተ ለወራት ባጠናው ጥናትና በሰበሰባቸው መረጃዎች መሰረት ማዕከላዊ እስር ቤት ውስጥ የሚገኙ ህንፃዎችን (የአስተዳደር ቢሮዎችን ሳይጨምር) በአራት ብሎክ እንከፍላቸዋለን። ማዕከላዊ ታስረው ከወጡ ንፁሐን ዜጎች በተገኘው መረጃ መሰረት የታሳሪዎቹን ማጎሪያ ክፍሎች በብሎክ ደረጃ ቅጽል ሥሞች ወጥቶላቸዋል። “ጨለማ ቤት” (ሳይቤሪያ)፣ “ጣውላ ቤት”፣ “ሸራተን” እና “ማዳም” (ለሴቶች ብቻ የተዘጋጁ ክፍሎች) በሚል መጠሪያ ተሰይመዋል።
ብሎክ አንድ፡- “ጨለማ ቤት” – ሳይቤሪያ ብሎክ
ምስሉን የሠራው ማዕከላዊ ጨለማ ክፍል ለወራት ሲሰቃይ የነበረው ጫላ ነው
የመጀመሪያውና እጅግ ዘግናኝ የሆኑ ቅጣቶች የሚፈፀምበት ብሎክ “ጨለማ ቤት” (ሳይቤሪያ) ተብሎ የሚጠራው ነው። የአካል ብቃታቸውን በስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች ባፈረጠሙ ቅልብ ወታደሮች የሚጠበቀው ይህ እስር ቤት፤ ጨለማ ክፍል ብቻ አስር የሚሆኑ ነጠላ ክፍሎች አሉት። ግራና ቀኙ (አምስት አምስት) በኮሪደር የተከፈለ ነው። ጨለማ ቤት የሚባለው በከፍተኛ ደረጃ በስቃይ የታጀበ ምርመራ የሚደረግባቸው ዜጎች የሚታጐሩበት ብሎክ ነው። ይሄው ብሎክ ፖለቲካ ነክ እሰረኞች ከሌሎች መሰሎቻቸው ተነጥለው ለብቻቸው የሚታሰሩባቸው ክፍሎችን የሚይዝ ነው። እነዚህ እስረኞች በአብዛኛው ከኦጋዴን፣ ከኦሮሚያ፣ ከጋምቤላና ከሰሜን ጎንደር ታፍነው የሚመጡ ንፁሐን ዜጐች ናቸው።  ጨለማ ቤቶች ፈፅሞ ብርሃን አልባ ናቸው። ለሌሊት ለጥበቃ ሲባል ከኮሪደሩ ላይ ተሰቅሎ አስሩንም ክፍል (ሳይቤሪያ – ጨለማ ቤት ብሎክ) ከሚያደርሰው አንድ የፍሎረሰንት መብራት ውጪ በክፍሎቹ መስኮት የሌላቸውና በሮቹ ተዘግተው የሚውሉ በመሆኑ፤ በክፍሎቹ የሚታሰሩ ዜጎች ቀንና ሌሊት በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ውለው ያድራሉ። በ24 ሰዓታት ውስጥ ለሽንት በሚፈቀዱ ጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ (በአብዛኛው የሌሊቱ አጋማሽ ላይ) ከክፍላቸው እንዲወጡ የሚፈቀድላቸው እስረኞች፤ መራመድ ተስኗቸው፣ አይናቸው ለሌሊት ጥበቃ የበራውን ባውዛ መቋቋም አቅቶት ተዝለፍልፈው ሲወድቁ ማየት የተለመደ ክስተት ነው።
“ጨለማ ክፍል” ውስጥ እንዲታሰሩ የሚደረጉ እስረኞች ከፍተኛ የሆነ አካላዊና ሥነልቦናዊ ጉዳት እንዲደርስባቸው የሚፈልጉ እስረኞች ናቸው። ከክፍሉ እርጥበት የተነሳ በእነዚህ ክፍል ሚታሰሩ እስረኞች እግራቸዉን ዘርግተዉ መቀመጥ አይችሉም። ለመቆም  ሲሞክሩም ባዶ እግራቸውን በመሆናቸዉ የወለሉ ቅዝቃዜ ለመቆም አቅም ይነሳል። እሰረኞቹ ያላቸዉ ብቸኛ አማራጭ ለረጅም ሰዓት በመቀመጫ (ኋላቸው) ወለሉ ላይ ተቀምጦ መቆየት ነው። በዚህ አሰቃቂ የእስር ውሎና አዳር ለረጅም ሰዓት ግርግዳ ተደግፎ መቀመጥ ከክፍሉ ቅዝቃዜ አኳያ ድብዳባዉ ታክሎበት የጀርባ ህመም (የዲስክ መንሸራተት) የሚያስከትል ይሆናል።
በዚህ የተነሳ በርካቶች ሙሉ አካል ይዘው ወደ ማዕከላዊ እስር ቤት ገብተው ከሥነልቦና ቁስሉ ባሻገር የአካል ጉዳተኛ ሆነው ይወጣሉ። ይህ ሁነት በምርመራ ወቅት በእስረኞች ላይ የሚደርሰውን አሰቃቂ ቶርቸር ሳይጨምር መሆኑን ልብ ይሏል።
ለማሳያነት የቀረበ
ከእስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መታወጅ በኋላ በአማካይ 6 በ 4 ካሬ ስፋት ባላቸው ጨለማ ቤቶች ውስጥ ከ20 – 25 የሚደርሱ እስረኞች መታጎር ጀምረዋል። ክፍሎቹ ድቅድቅ ጨለማ በመሆናቸው ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ የሚታሰብ አይደለም። በጊዜ ቆይታ ብዛት አዕምሯቸው ማስታወስ የተሳነው፣ የአዕምሮ መቀወስና ጭንቀት የወጠራቸው እስረኞች በሚችሉት ቋንቋ የብሶት ዜማ ሲያሰሙ፣ ሲራገሙ፣ ሲሳደቡ፣… ውለው ያድራሉ። ጨለማ ክፍሎች መስኮቶች የሌላቸውና በራቸው ዝግ የሆኑ ግንብ ቤቶች በመሆናቸው ድምፅ አያስወጡም። በጨለማ ክፍሎች ተላላፊ በሽታዎች በተለይም ተቅማጥ፣ ትውከት፣ እከክ፣ … የተለመዱ ናቸው። ከምግብ ንፅህና ጉድለት ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ ታይፈስና ታይፎይድም በእስረኞች ላይ ተፈራራቂ በሽታዎች ናቸው። በጨለማ ክፍል የታሰሩ እስረኞች በቀን ሁለት ጊዜ አምስት ሰዓት እና ምሽት አንድ ሰዓት ላይ “ምግብ” ባሉበት ክፍል ይቀርብላቸዋል።
በ24 ሰዓት አንድ ጊዜ ብቻ ለሽንት ወደ ውጪ የሚወጡ በመሆኑ የተቅማጥና ትውከት በሽታ የያዛቸው እስረኞች በየሰዓቱ በጨለማ ክፍል ውስጥ ሊፀዳዱና ሊያስታውኩ ይችላሉ። አስከፊው ነገር ጨለማ ክፍሎቹ የማይፀዱ መሆናቸው ነው። ጉንፋንና ሳይነስ ተከታይ በሽታዎች ናቸው። የትውከቱና የፅዳጁ (ሰገራው) ሽታ መፈጠርን ያስጠላል። አንዱ እስረኛ ሌላውን እስረኛ እንዳያግዘውና እንዳይደግፈው ክፍሎቹ ድቅድቅ ጨለማ የዋጣቸው ናቸው። ከዚህም አልፎ ጨለማ ክፍሎች ውስጥ የመግባቢያ ቋንቋ ችግር በመኖሩ በዝምታ መዋጥ፣ የራስን ጩኽት ብቻ ማስተጋባት ተፈራራቂ ክስተቶች ናቸው።
“ጨለማ ቤት” – ሳይቤሪያ ብሎክ ውስጥ የተመረጡ እስረኞች ለብቻቸው ይታሰራሉ። በተለይም በኦብነግ፣ ኦነግ እና አርበኞች ግንቦት ሰባት አባላት መልማዮችና የከተማ ሽብር አመራር ሰጪ በሚል ተጠርጥረው የሚያዙ ዜጎች ለብቻቸው ይታሰራሉ። እንዲህ ባሉ የብቻ እስር ክፍሎች ከማቀቁትና ከሚማቅቁት ከፖለቲካ እስረኞች በተጨማሪ የኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት የዚህ መሰል አሰቃቂ እስር ሰለባ ነበሩ።
ብሎክ ሁለት፡- ጣውላ ቤት
ሁለተኛው ክፍል ወለሉ ላይ ከተነጠፈው ጣውላ ስሙን ያገኘው “ጣውላ ቤት” የሚባለው ነው። በዚህ ብሎክ ውስጥ በአንድ ረድፍ አምስት ክፍሎች አሉ። በእነዚህ ክፍሎች በቀደሙት ጊዜያት ከ5 – 8 ድረስ እስረኞች ይታሰሩ ነበር። በኦሮሚያና በአማራ ክልል ከተነሳው ህዝባዊ አመፅ በኋላ በእነዚህ ክፍሎች የታሳሪዎች ቁጥር በእጥፍ ጨምሯል። በተለያዩ ተባዮች በተወረረው በነዚህ ክፍሎች ውስጥ መስኮቶቹ ለረጅም ሰዓታት የሚዘጉ ከመሆናቸው በላይ ግርግዳዎቻቸው ቅዝቅቃዜን ከሚያመጡ አለቶች የተገነቡ በጣም ጠባብ ክፍሎች ናቸው። በእነዚህ ክፍሎች የታሰሩ እስረኞች በቀን ሁለት ጊዜ ለሽንት እንዲወጡ ይደረጋል። በክፍሎቹ ውስጥ ሆነው በበሩ በኩል ወደ ውጭ ቢጣሩ ሰሚም ያገኛሉ። የጣውላ ቤት እስረኞች ከጨለማ ቤት – ሳይቤሪያ እስረኞች አያያዝ አኳያ የተሻለ ነው ቢባልም ጣውላ ቤት ክፍሎች በተባይ የተጠቁ ናቸው።
ለማሳያነት የቀረበ
በእነዚህ ክፍሎች የሚታሰሩ ታሳሪዎች የፖለቲካና የህሊና እስረኞች እንዲሁም የዩኒቨርስቲ ተማሪ ሆነው በተለያዩ ጊዜያት የሚታሰሩ ዜጎች ይገኙባቸዋል። በግድያና በዘረፋ ወንጀል ተጠርጥረው የሚታሰሩ ዜጎችም በነዚህ ክፍሎች ይገኛሉ። እነዚህ እስረኞች ተጠርጥረው የታሰሩበት የ“ወንጀል” ክብደት መጠን ከጨለማ ክፍል እስረኞች ጉዳይ (Case) አኳያ መካከለኛ የሚባል ነው። አሰቃቂውን የምርመራ ሂደት በ24 ሰዓት ውስጥ ሁለትና ሦስት ጊዜ ወደ ምርመራ ቢሮና ቶርቸር ክፍል እየተወሰዱ አሳራቸውን ይበላሉ። የጣውላ ቤት እስረኞች ከቶርችር አከሉ ምርመራ በኋላ ወደ ክፍላቸው ተደግፈው ሲመለሱ አንፃራዊ “የአይዞህ” ባይነት ድጋፍ ከታሳሪዎች እንደ ቋንቋ መግባቢያቸውና በምልክት ቋንቋ ድጋፍ ይሰጣጣሉ።
በጣውላ ቤት ክፍሎች ቫዝሊንና መሰል የቆዳ ቅባቶች እንዲሁም ፋሻ ጨርቆች የአልማዝ ዕንቁ ያህል ውድ ናቸው። በድብደባ የደቀቀ ሰውነታቸውን የሚጠግኑት በእነዚህ ቅባቶችና ፋሻ ጨርቆች አማካኝነት ነው። ፋሻ ጨርቅ ብዙ ጊዜ የማይገኝ በመሆኑ የቲሸርትና ሸሚዝ ቅዳጅ ጨርቆች የእስረኞች ቁስልና በድብደባ የተፈጠሩ የሰውነት እብጠቶችን ለማሰር ይጠቀሙባቸዋል።
በነገራችን ላይ ማዕከላዊ እስር ቤት ውስጥ በአሰቃቂ ነፍስ ግድያ፣ በሙስና፣ በአራጣ፣ በከባድ ወንጀል ዘረፋ፣… የተጠረጠሩ ዜጎች ጣውላ ቤት ክፍሎች ሲታሰሩ፤ የኦብነግ የኦነግና የአርበኞች ግንቦት ሰባት አባል ናችሁ፣ በህገ ወጥ ሰልፎች ተሳትፋችኋል ወዘተ በሚል ያለአንዳች የሰውና የሰነድ ማስረጃ ጨለማ ክፍሎች – ሳይቤሪያ ውስጥ ከአሰቃቂ የምርመራ ሂደት ጋር ለወራት የሚታሰሩ ወጣቶች በርከት ያሉ ናቸው።
ለማሳያነት የቀረበ
ብሎክ ሶስት፡- ሸራተን
በአንፃራዊነት ካለው “ምቾት” አኳያ “ሸራተን” ተብሎ የሚጠራው ይህ ብሎክ፤ አልፎ አልፎ ምርመራቸውን ጨርሰዋል የሚባሉ እስረኞች ወደ ቂሊንጦ ከመውረዳቸው በፊት ቆይታ ያደርጉበታል። ከፖለቲካ ጋር ምንም ዓይነት ንክኪ በሌላቸው ወንጀሎች የተጠረጠሩ እስረኞችም ይቆዩበታል። በ“ሸራተን” ውስጥ እስረኞች ውሃም ሆነ ምግብ ከቤተሰብ ያገኛሉ። የቤተሰብ ጠያቂና የህግ አማካሪም ይጎበኛቸዋል። እንደ ትራስ፣ የሌሊት ልብስ፣ ሶፍት፣ ማህረም፣ ሳሙና፣ … ያሉ የ“ቅንጦት” ዕቃዎች “ሸራተን” ውስጥ ተፈለገው አይጠፉም። የ“ሸራተን” እስረኞች የጨለማ ክፍል – ሳይቤሪያ እስረኞች ጋር ፈፅሞ እንዲተያዩ አይፈቀድላቸውም። ለዚህም ነው የጨለማ ክፍል – ሳይቤሪያ እስረኞች በ24 ሰዓት ውስጥ አንድ ጊዜ የሌሊቱ አጋማሽ ላይ ለሽንት እንዲወጡ የሚደረገው። በአንፃሩ የ“ሸራተን” እስረኞች በቀን ሁለት ጊዜ ለሽንት እንዲወጡ የሚደረግ ሲሆን፤ ከዚህ በተጨማሪም የቤተሰብ መጠየቂያ (መጎብኛ) ፍቃድ አላቸው።
ከጨለማ ክፍል – ሳይቤሪያ የእስረኞች አያያዝ አኳያ ይህኛው ክፍል የተሻለ በመሆኑ “ሸራተን” የሚል ስያሜ እስረኞቹ ቢሰጡትም በዚህ ብሎክ ተጨማሪ የመብት ጥያቄ የሚያነሱ እስረኞች ወደ ጨለማ ክፍል ለሳምንታት ያህል ይወረወራሉ።
ብሎክ አራት “ማዳም” የሴቶች ብቻ ክፍል
ለማሳያነት የቀረበ
በማዕከላዊ እስር ቤት በአንፃሩ ሴት ታሳሪዎች ከወንዶች የተሻለ ለብቻቸው በተከለለው ቦታ የመንቀሳቀስ ዕድል ቢኖራቸውም በአንድ ጠባብ ክፍል ውስጥ እስከ 70 የሚደርሱ እስረኞች ይታሰራሉ። ሴት እስረኞች እንደተጠረጠሩበት የወንጀል አይነት አያያዛቸው ይለያያል።
ህወሓት በከሳሽነት በሚቀርብባቸው ጉዳዮች የሚታሰሩ ሴት እስረኞች ለብቻቸው ጨለማ ክፍል የሚታሰሩበት አጋጣሚ አለ። ከዚህ ጋር በተያያዘ የቀድሞዋ ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ፣ ጦማሪት ማህሌት ፋንታሁንና ኤዶም ካሳሁን እንዲሁም ፖለቲከኛ እማዋይሽ በማዕከላዊ የእስር ቆይታቸው የደረሰባቸው አሰቃቂ የምርመራ ሂደትና የእስር አያያዝ አስረጅ ምሳሌዎች ናቸው። ሴት እስረኞችን በውድቅት ሌሊት በወንድ መርማሪ ፖሊሶች ብቻ እንዲመረመሩ ማድረግ፣ ከባድ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ እንዲሰሩ ጫና መፍጠር፣ ራቁታቸውን በመርማሪ ፖሊሶች ፊት እንዲቆሙ ማድረግ፣ ለወራት በጨለማ ክፍል በማቆየት ከሴትነት ተፈጥሯዊ ግዴታ ጋር ተያይዞ በሚመጣ ፈሳሽ ሰውነታቸው እንዲቆሽሽ ማድረግ፤ ውሃ እንኳ መከልከልና ተያያዥ የማሰቃያ ስልቶች በሴት እስረኞች ላይ የሚፈፀሙ በደሎች ናቸው። ከዚህም ባለፈ ሴት እስረኞች ወደ አደባባይ ሊያወጧቸው የሚከብዷቸው ድርጊቶች በሴትነታቸው ላይ እንደተፈፀመ/እንደሚፈፀም የጎልጉል ዳሰሳ ጥናት ውጤት ያመለክታል።
የቶርቸር አይነት በማዕከላዊ . . .
ህወሓት “ሕገ – መንግስቱን በኃይል ለመናድ ሲንቀሳቀሱ አገኘኋቸው” በሚል ወደ ማሳሪያ ቦታ የሚወረውራቸው ንፁሐን ዜጎች ላይ መረጃ ለመሰብሰብ በሚል በአካላቸው ላይ ከፍተኛ ስቃይ እና እንግልት እንደሚያደርስባቸው ዓለምአቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅቶች በተደጋጋሚ የሚያወጡት ሪፖርት ያመለክታል። ለዚህ አሰቃቂ የምርመራ ዘዴ የፖሊስ ኃይሉን፣ የእስር ቤት መርማሪዎችንና ወታደራዊ ኃይሉን ጨምሮ የተለያዩ የፀጥታ ኃይሎችን በሙሉ ኃይሉ ይጠቀማል።
ማዕከላዊ እስር ቤት ደግሞ በተለየና በተጠና አደረጃጀት የተዋቀረ የ“ወንጀል ምርመራ” ፖሊስ ጣቢያ ነው። ጣቢያው በትግራይ ተወላጆች የበላይነት የሚመራ የዘመናችን የግፍ ጎሬ ነው። “መርማሪ” ተብለው የሚመደቡ ፖሊሶች በ“ምርመራ” ውጤታቸው ሊደርሱበት የሚገባ ጭብጥ አስቀድሞ ይሰጣቸዋል። ተጠርጣሪ ወንጀለኛው “መርማሪ” ፖሊሶች የሚጠይቁትን እየተከተለ አውንታዊ ምላሽ ብቻ እንዲመልስ ይገደዳል። “የምሻውን በልልኝ” አይነት ነገር መሆኑ ነው። ከዚህ ባፈነገጠ መልኩ ተጠርጣሪ ወንጀለኛው የራሱን እውነት የሚናገር ከሆነ የተዘጋ ጭንቅላት፤ ራሮት የራቀው ልቦና ያላቸው “መርማሪዎች” ምህረት የለሽ ስቃይና ድብደባ መፈፀም ይጀምራሉ።
  1. በማዕከላዊ እስር ቤት በኤሌክትሪክ ገመድ መገረፍ፣
  2. እጅና እግር አሰቃቂ በሆነ መልኩ ለረጅም ጊዜያት በሰንሰለት መታሰር፣
  3. ጭንቅላትን በበርሚል ውስጥ ባለ ቀዝቃዛ ውሃ መዘፍዘፍ፣
  4. የወንዶች ብልት ላይ እስከ አንድ ሊትር የሚደርስ የጠርሙስ ውሃ ማንጠልጠል፣
  5. የተጠርጣሪውን እጆች የኋሊት ጠፍሮ በማሰር ብልቱ ላይ የበቀለውን ፀጉር በክብሪት መለብለብ (ማቃጠል)፣
  6. ጥቁር የተወጠረ ወፍራም ላስቲክ በሆነው ቻይና ሰራሽ የፖሊስ ዱላ የተጠርጣሪ ወንጀለኛውን አካል ሳይመርጡ መደብደብ፣ … ወዘተ
    ለማሳያነት የቀረበ
የመሳሰሉት የቶርቸር አይነቶች በ“ምርመራ” ሰዓት በተጠርጣሪ ወንጀለኞች ላይ የሚደርሱ የስቃይ አይነቶች ናቸው። ከነዚህ ከባድ የስቃይ አይነቶች በተጨማሪ የተጠርጣሪ ወንጀለኞች ዘውጋዊና ሐይማኖታዊ ማንነት እየተጠቀሰ በ“መርማሪ” ፖሊሶች የሚደርሰው ስድብ እስረኞቹ የማይሽር ጠባሳና ቂም ይዘው እንዲወጡ ያደርጋቸዋል።
“ሽንታም አማራ”፣ “ደንቆሮ ኦሮሞ”፣ “ጉራጌ ንግድ እንጂ ፖለቲካ ታውቃለች?” “አጨበርባሪ ጉራጌ”፣ “በእንግድነት መጥታችሁ እንገስ አላችሁ”፤ “መጤ የአረብ ርዝራዥ”፣… እየተባሉ የተሰደቡ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች፣ የሙስሊሙ ማህበረሰብ ተወካዮች (ኮሚቴዎች) ከወረደባቸው ዱላ በላይ የተሰደቡት ስድብ ሲያማቸው ይኖራል። የማዕከላዊ ስቃይ ተሸካሚዎች ጊዜና ትውልድ እስከሚከሳቸው ድረስ ቂማቸው የሚሽር አይመስልም።
በቀጣይ ዕትማችን በማዕከላዊ እስር ቤት በ“መርማሪ” ፖሊሶች የሚፈፀሙ በደሎችንና አሰቃቂ ቶርችር የተፈፀመባቸውን ዜጎች የኋላ ማንነትና የስቃይ ሁኔታ ለማሳያነት እናቀርባለን።
(ፎቶ – የመግቢያው ፎቶ የተወሰደው ከዚህ ላይ ነው። ሌሎቹ ፎቶዎች ከማዕከላዊ የወጡ ሳይሆን ለማሳያነት የቀረቡ ናቸው።)

No comments:

Post a Comment