Translate

Saturday, August 16, 2014

''አማራጭ የሌለው ምርጫ''

ሄለን ንጉሤ

ከኖርዌ

አንድ ሀገር እንደ ሀገር ለመቀጠል የሚያስችላትን ትልቁን ድርሻ የመወጣት ኃላፊነት ያለበት በስልጣን ላይ ያለው ስርአት ነው። ሥርዓቱ የሐገሪቱን ህገ መንግስት በመፈፀምና በማስፈፀም ህገ መንግስቱ ሳይሸራረፍና ሳይጣስ እንዲሁም ዜጎች ህገ መንግስታዊ መብቶቻቸውን ያለ አንዳች መድልኦ በመጠቀም በፍርድ ቤት የመከሰስና የመክሰስ፣ የመርታትና ያለመርታት መብታቸው ተከብሮ በሐገሪቱ የህግ የበላይነት ተረጋግጦ መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን ለማድረግ በስልጣን ላይ ያለው ስርአት ወሳኝነት አለው።  በአንፃሩ ደግሞ በስልጣን ላይ ያለው ስርዓት ይህንን ማስፈፀም ካልቻለና ሆን ብሎ የሐገሪቱን ልዑአላዊነት ላለማስጠበቅ የሚሰራ ከሆነ ዜጎች እንደዜጋ የራሳቸውን መብት ማስጠበቅና በሐገራቸው መልካም አስተዳደር የማስፈን ግዴታ ያለባቸው ለመሆኑ ምንም አይነት ጥያቄ የማያስፈልገው የዜግነት ግዴታ መሆኑ በግልፅ ሊታወቅ ይገባል።

ኢትዮጵያ ሀገራችን አሁን ያለችበት ተጨባጭ ሁኔታ ቁልጭ አድርጎ እንደሚያሳየው በሀገሪቱ ላይ ያለው ባንዳ አምባገነን ቡድን ሀገሪቱን የሚጠቅም አንዳች ስራ ባለመስራቱ ሀገሪቱ በከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ትገኛለች። እንደአለመታደል ሆኖ ሳይሆን ሆን ተብሎ በወያኔ ዘረኛ አምባገነን ሥርዓት በተያዘ ሀገር የማፈራረስ ሴራ ሀገራችን አሁን ላለችበት ደረጃ ተዳርጋለች። እንደ ሀገር እንኳን መቀጠል ከማይችሉ ሀገራት ተርታ አንዷ ሆና መገኘቷንም የቅርብ ጊዜ ጥናቶች ያሳያሉ። ዜጎቿን አፍና የምትበላ ሰው መሳይ አውሬዎች የሚያስተዳድሯት ሀገር ሆናለች።

በሀገሪቱ መንግስትን መተቸት በፍፁም የማይታሰብ ሲሆን ጋዜጠኞች ነፃ ሐሳባቸውን ማንሸራሸርና ትክክለኛ መረጃን ለህዝብ ማቅረብ ተስኗቸዋል። ያለው የአፈና ሥርዓት በግል የሚሰሩ ጋዜጠኞችን እና ፀሐፊዎችን እያደነ ለእስርና ለግርፋት፣ ለመከራ የሚዳርግ በመሆኑ ጋዜጠኞች እና ፀሐፊዎች ይሄ እጣ ፈንታቸው መሆኑን አውቀው መከራውን እየተቀበሉ ይገኛሉ። እስርና እንግልቱን መሸከም ያቃታቸው ደግሞ የሚወዷትን ሀገራቸውንና  የሚወዱትን ሞያቸውን ትተው ነፍሳቸውን ለማትረፍ እየተሰደዱ ይገኛሉ።

አምባገነኑ ወያኔ ህገ መንግቱን ወደ ህገ አራዊት ቀይሮ ዜጎችን ለማሰቃያ እየተጠቀመበት ይገኛል። ለዚህም ማሳያ በህጋዊ መንገድ ተደራጅተው የሚገኙ የፖለቲካ ድርጅቶችን ያሰጉኛል ብሎ ያሰባቸውን በሙሉ በፀረ-ሽብር ህግ እየከሰሰ ያለምንም ማስረጃና መረጃ ለእስርና ለስቃይ ዳርጓል። ሌሎችም የተቃዋሚ ድርጅት አባላት በሰው በላ ደህንነቶቻቸው በየመንገዱ ተገድለዋል። የእስልምና ሐይማኖት ተከታዮች ተደብድበዋል ተገለዋል ሴቶች እህቶቻችንን ሂጃባቸውን አስወልቀው በመግረፍ ለዜጎች ያላቸውን ንቀት በአደባባይ አሳይተዋል። ህዝቡን በዘር በማጋጨትና በመከፋፈል ጥላቻን በህዝቡ መሃል ለመዝራት ከፍተኛ የካድሬ ስራ ሰርተዋል። የአንድ ዘር የበላይነት አስጠብቀው ሌላው በሃገሩ እንደሌላ ዜጋ አንገቱን ደፍቶ እንዲሄድ በዘሩ እየተንቋሸሸ እየተሰደበ፣ ከቀዬው እየተፈናቀለ ይገኛል። በሀገር ውስጥ የሚደርሰውን በደል መዘርዘር ጊዜ አይበቃም ሁሉም የሚያውቀው ነው ግን ይሄ እስከ መቼ ይቀጥላል መቼ ነው የሚያቆመው ብለን ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል።

ወያኔ በሀገር ውስጥ የሚያደርሰው በደል አልበቃ ብሎት በውጪ ተሰዶ የሚኖረውን ስደተኛ የሀገሪቷን ከፍተኛ ገንዘብ ለስለላ በማዋል ከተለያዩ የጎረቤት ሀገሮች ጋር ተባብሮ የዱርዬ ስራ በመስራት ስደተኞችን እያፈኑ መውሰድ የተለመደ ስራቸው ሆኗል። በቅርቡ ደግሞ እጃቸውን ትንሽ ረዘም አድርገው አለም አቀፍ ህግን በሚፃረር መልኩ የግንቦት 7 የፍትህ የነፃነትና የዲሞክራስ ንቅናቄ ዋና ፀሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ከየመን ታፍነው ተወስደው ሰው ባልሆኑ አውሬ የደህንነት ሰዎች ከፍተኛ ስቃይ እየደረሰባቸው መሆኑ ይታወቃል። አቶ አንዳርጋቸው የታላቋ ብሪታኒያ ዜግነት ያላቸው ቢሆንም እስከአሁን ድረስ ማንም እንዲጎበኛቸውም ሆነ የህግ አማካሪ እንዳያገኛቸው ተደርገው በአስቸጋሪና ከባድ በተባለ የማሰቃያ ዘዴዎች በመጠቀም እያሰቃዩአቸው ይገኛሉ።

ወያኔ በ23 አመታት የአገዛዝ ዘመኑ ሲገዛን የኖረው በራሳቸው መተማመን በማይችሉ ባልተማሩና ሀገር ቀርቶ  መንደር ማስተዳደር የማይችሉ አናሳ አስተሳሰብ ባላቸው የአምስተኛ ክፍል ተማሪዎች ሲሆን እነኚህ የአምስተኛ ክፍል ተማሪዎች ሰላማዊ ትግል የሚባል ነገር ስለማይገባቸው የተደረጉትን የሰላማዊ ትግሎች በሙሉ በማጨናገፍ የትግሉን አቅጣጫ እራሳቸው ወደ ለመዱት ሜዳ ቀይረውታል።  በሰላማዊ መንገድ ለውጥ እናመጣለን ብለው በየዋህነት በሀገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎችን በሙሉ በአሸባሪነት እየከሰሱ ወደ ማእከላዊና ቃሊቲ እያጎሩ ይገኛሉ። ወያኔ በሰላማዊ መንገድ ስልጣን ያሰረክባል ብሎ ማሰብ የዋህነት መሆኑን እራሳቸው በስራቸው እየመሰከሩልን ነው።

እንግዲህ በሰላማዊ ትግል ለውጥ ይመጣል ብለን ሌላ 23 አመት የምንጠብቅ ከሆን የዋሃን ብቻ ሳንሆን ጅሎች መሆናችንን ማወቅ አለብን። ወያኔ የትግሉን አቅጣጫ እንድንቀይር የሚያስገድደንን እጅግ በርካታ በደሎችና  ግፎች አድርሶብናል። ትከሻን መሸከም ከሚችለው በላይ ተሸክመን ጎብጠናል ቀና ብለን መሄድ ያስፈልገናል። ቀና ብለን ደረታችንን ነፍተን ለመሄድ ደግሞ ትከሻችንን የተጫነንን ነገር ከላያችን አውርደን መጣል ይኖርብና።  በደል በቃኝ፣ እስር በቃኝ፣ ግርፋት በቃኝ፣ እንግልት በቃኝ፣ ስደት በቃኝ፣ ዘረኝነት በቃኝ፣ እምቢኝ ማለት ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። ይህንን ከልባችን ተሰምቶን ካልንና የሰላማዊ በሮች መዘጋታቸውን ካወቅን አማራጭ ያጣንለትን ምርጫ መውሰዳችን ግድ ይሆናል።

ማንም ሰው የሰላም አማራጮችን አጥብቆ የሚፈልግ ቢሆንም ወያኔ በሰላም ስልጣን እንደማያስረክብ ደጋግሞ ነግሮናል እንደውም ይሞክሩኝ አይነት ንግግሮችንም በተደጋጋሚ አሰምተውናል ስለሆነም እነሱ በመረጡት መንገድ ሀገራችንን ከወያኔ የውስጥ ወራሪ ነፃ ለማውጣት የትጥቅ ትግሉ የግድ መሆኑ የማይቀር አማራጭ የሌለው ምርጫ በመሆኑ የትጥቅ ትግሉን መደገፍ ያስፈልገናል። የትጥቅ ትግሉን ውድ ህይወታችንን ገብረን፣ አጥንታችንን ከስክሰን፣ ደማችንን አፍስሰን፣ ሀገራችንን ከወያኔ ስርአት ነፃ እናወጣለን የህዝባችን ራእይ እውን እንዲሆን እንታገላለን ብለው ጫካ ገብተው መሬት ላይ የወረደ ስራ እየሰሩ ያሉ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን የትግሉን መስመር ጀምረውልናል። እኛ ሁላችንም ሀገራችን በህዝቦችዋ በተመረጡ መሪዎች የምትተዳደር እንድትሆን፣ የህግ የበላይነት የሚከበርባት ሀገር እንድትሆን፣ የዜጎች የሰብአዊ መብት የሚከበርባት፣ ዜጎች ያለ አንዳች መድልኦ በእኩል የሚተዳደሩባት፣ በጥቅሉ የመልካም አስተዳደር ባለቤት የምትሆንባት ዜጎቿ የማያፍሩባትን ሀገር ለመመስረት ሁላችንም አስተዋፅኦ ማበርከት ይኖርብናል። ትግሉን ወደፊት ለማራመድ ብቻ ሳይሆን ትግሉን ጫፍ ለማድረስ ጭምር ለራሳችን ቃል ገብተን ትግሉን መቀላቀል የምንችል ትግሉን በመቀላቀል የማንችል ደግሞ ትግሉን በምንችለው ሁሉ በማገዝ ሀገራችንን ከአምባገነንኖች ነፃ ማውጣትና አዲሲቷን ኢትዮጵያ መመስረት መቻል አለብን።

የትጥቅ ትግል ዋናው አስፈላጊነቱ እነኚህ ባንዳ የባንዳ ልጆች ከስልጣን በጠመንጃ እንጂ በሰላማዊ መንገድ አንለቅም በማለታቸውና ሀገራችን ኢትዮጵያ እንደሀገር መቀጠል ስላለባት ሳትፈራርስ በፊት የግድ የስርአት ለውጥ  አስፈላጊ በመሆኑ አማራጭ የሌለው ምርጫ የትጥቅ ትግሉ ግድ ይላል!!

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

No comments:

Post a Comment