Translate

Monday, November 5, 2012

ከሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች

Adigrat
የአዲግራት ወህኒ ቤት ተደረመሰ
በትግራይ ክልል ካሉት እስር ቤቶች መካከል ከ1‚300 በላይ የሚሆኑ የሕግ እስረኞችን የያዘው የአዲግራት ወህኒ ቤት ባለፈው ረቡዕ ተደርምሶ 14 እስረኞች ሲሞቱ፣ ከ35 በላይ ደግሞ በከባድ ሁኔታ መጎዳታቸውን ሪፖርተር ምንጮች እንደነገሩት ጠቅሶ አስታወቀ። እስር ቤቱ በምን ምክንያት እንደተደረመሰ ያልገለጸው ሪፖርተር እስረኞቹን ለማትረፍ ሦስት ሎደሮችና በርካታ ወታደሮች ሲረባረቡ ማየታቸውን አመልክቷል።

አደጋው ቀን ረፋድ ላይ መድረሱ በጀ እንጂ አደጋው የከፋ ሊሆን እንደሚችል ተዘግቧል። ተረፉ የተባሉት 35 ሰዎች ክፉኛ በመጎዳታቸው አዲግራት ሆስፒታል ተኝተዋል። ህይወታቸው ያለፈው 14 እስረኞች ግን ከፍርስራሹ መቀበራቸውን የሪፖርተር ዘገባ ያስረዳል። የመከላከያ ሰራዊት አባላት ያደረጉት በዶዘር የተደገፈ ርብበርብ በህይወት የተረፉትን ነፍስ እንደታደገ ተጠቁሟል። አደጋው መድረሱን የትግራይ ክልል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ጽ/ቤት አስተዳደር ማመኑን ጋዜጣው አስታውቋል።
በሌላ በኩል ይህንኑ ዜና በአዲግራት እስር ቤት የደረሰው አደጋ ከፈንጂ ጋር በተያያዘ ጥቃትና አደጋ እንደሆነ የተለያዩ ድረ ገጾች ዘግበዋል። በዘገባውም መሠረት የኢትዮጵያ አንድነት፣ ነጻነት ኃይል የተሰኘው ቡድን ስለደረሰው ጥቃት ኃላፊነቱን ስለመውሰዱ አብሮ ተዘግቧል፡፡ የኢትዮሚዲያ ድረገጽ ከቡድኑ ቃልአቀባይ ጋር በስልክ መገናኘቱንና በቃልአቀባዩ መሠረት እስረኞቹ በ1997 የምርጫ ወቅት ከጎንደር፣ ጎጃም፣ አዲስአበባ ሌሎች ቦታዎች ተጥዘው የታሰሩ መሆናቸውን ዘግቧል፡፡ የታሰሩና የአደጋውን ትክክለኛ መንስዔ በተመለከተ ከመንግስት የተባለ ነገር የለም።
በአስር ዓመት ጊዜ ውስጥ 15 ቢሊዮን ዶላር እንዲሸሽ ተደርጓል
የማሳቹሴትስ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ኢኮኖሚ ምርምር አንስቲትዩት ይፋ እንዳደረገው ከኢትዮጵያ የሚሸሸው የውጪ ምንዛሬ ባለፉት አስር ዓመታት ብቻ አስራ አምስት ቢሊዮን ዶላር ደርሷል።
እንደ ጥናቱ ካፒታል የማሸሽ መጠኑ እ.ኤ.አ. ከ2001 ጀምሮ በ2.1 ቢሊዮን ዶላር እየተመነደገ መምጣት ሲጀምር፣ 2002፣ 2003፣ 2004፣ 2007፣ 2009 እንዲሁም 2010 ላይ በእያንዳንዱ ዓመት የ1.4 ቢሊዮን ዶላር መጠን የመዘገበበት የገንዘብ መጠን ከአገሪቱ ወጥቷል፡፡
ሪፖርቱ ያካተታቸው ጊዜያት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን የመጨረሻዎቹ አራት ዓመታት፣ እንዲሁም የደርግን የመጨረሻዎቹ አሥር ዓመታት ሲሆን፣ በእነዚህ ጊዜያት ከተመዘገበው የገንዘብ ማሸሽ በልጦ የተገኘው ግን ባለፉት አሥር ዓመታት የተመዘገበው መጠን ነው፡፡
እ.ኤ.አ. በ1982 ከአገሪቱ የወጣው የገንዘብ መጠን 2.8 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን፣ ይህም ከፍተኛው በመሆን ተመዝግቦ የቆየ መጠን ነበር፡፡ ይህ ቢባልም በ1981 1.5 ቢሊዮን ዶላር፣ በ1985 1.3 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም በ1987 1.9 ቢሊዮን ዶላር በመውጣቱ ይህንን ጊዜ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከአገሪቱ የሸሸበት ሁለተኛው ዘመን እንዲሆን አስችሎታል፡፡
ከሰሐራ በታች ከሚገኙ 33 አገሮች በአጠቃላይ 814 ቢሊዮን ዶላር የሸሸ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 591 ቢሊዮን ዶላሩ በዚሁ ቀጣና ከሚገኙ ነዳጅ አምራች አገሮች እንዲወጣ የተደረገ ነው፡፡ ይህን ያህል መጠን ካፒታል እየሸሸ የሚገኘው ደግሞ የአገሮቹ የነዳጅ ገቢ እያደገ በመጣበት ጊዜ ሆኖ ሲመዘገብ፣ በተለይ ናይጄሪያ 311.4 ቢሊዮን ዶላር የሸሸባት ትልቋ አገር ሆኖ ተገኝታለች፡፡
እየሸሸ የሚገኘው ካፒታል በቀጣናው በይፋ የተሰጠውን 659 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም ከውጭ በቀጥታ ከተገኘው የ306 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት በልጦ መገኘቱ ሁነቱን አስገራሚ አድርጎታል። ሪፖርተር ይህንን ዘገባ ትኩረት ሰጥቶ አሁን ይፋ ቢያደርገውም ፋይናንሺያል ኢንተግሪቲ በተመሳሳይ ከኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ እንደሚጋዝ ሪፖርት ማቅረቡን ተከትሎ በውጪ አገር የሚኖሩ ባለሙያዎች፣ በውጪ አገር የሚዘጋጁ፣ የተለያዩ የአገር ውስጥና የውጪ አገር ሚዲያዎች መዘገባቸው አይዘነጋም። መንግስትም ሆነ አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ጊዜ ይህንን ሪፖርት በይፋ አላስተባበሉም።
ባህር ከ70 በላይ ኢትዮጵያዊያንን በላ
ከሶማሊያ ወደ የመን ሲጓዙ የነበሩ ስደተኞች በድንገት በተነሳ ማዕበል የተሳፈሩባቸው ጀልባዎች ውስጥ እንዳሉ መስጠማቸው ተሰምቷል። በአደጋው ከሰባ በላይ ወገኖች ህይወታቸው ያለፈ መሆኑን የየመን ባለስልጣናት ናቸው የተናገሩት።
በሁለት ጀልባዎች የኤደን ባህረ ሰላጤን ሲያቋርጡ ህይወታቸው ያለፈው ዜጎች አስከሬን ባህሩ ላይ ሲንሳፈፍ ታይቷል። ኢትዮጵያዊያን ከሶማሊያ ወደ የመን ለማቋረጥ እንደ ከብት ላይ በላይ ታጉረው ሲጓዙ በተመሳሳይ ህይወታቸው ያለፈው በተደጋጋሚ ነው። በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ደቡብ አፍሪካ በሚሄዱ፣ ወደ እስራኤል ለመጓዝ ሲና በረሃን በሚያቋርጡና በስደት ባሉበት ምድር ኢትዮጵያዊያን ላይ የሚደርሰው አደጋናመከራ የብዙ ዜናዎች መክፈቻ መሆኑ ህሊናን የሚጎዳና እስከመቼ የሚል ጥያቄ በየቦታው እየቀሰቀሰ ነው።
ፍቅሩ ተፈራ ለምን አይመረጥም?
የኢትዮጵያ የሴቶች ብሄራዊ ቡድን የደረሰበት ሽንፈትና አቋም በመንግስት መገናኛዎች ሳይቀር ተወገዘ። ቡድኑ አጨዋወቱና የተከተለው ስልት ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት የሌለው እንደሆነ ተጠቁሟል። ይህንኑ የሴቶች ሽንፈት ተከትሎ በቂም ሳቢያ ያልተመረጠው ፍቅሩ ተፈራ ለወንዶች ብሄራዊ ቡድን እንዲጠራ እየተጠየቀ ነው።
ባደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች ስምንት ግብ የተቆጠረባቸው ሉሲዎች ያስመዘገቡት ውጤት በወንዶችም አፍሪካ ዋንጫ ላይ ሊደገም እንደሚችል ከወዲሁ ስጋት ፈጥሯል። ከሰላሳ አንድ ዓመት አፍሪካ ዋንጫ መመለሳችን ያስደሰታቸው ወገኖች ደንግጠዋል። ጠንካራ አቋም እንዳላቸውና የምድብ ማጣሪያውን ማለፍ እንደማይሳነው የተነገረለት የሴቶች ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ አብርሃም ተክለሃይማኖት ሊባረሩ እንደሚችሉ ፍንጭ የሰጠው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ስፖርት ዝግጅት ክፍል ለመጀመሪያ ጊዜ “በታላላቅ ውድድሮች ለመወዳደር መብቃት ብቻውን በቂ አይደለም። ብቁ ተወዳዳሪ መሆን ያስፈልጋል” ብሏል።
አስተያየት ሰጪዎች እንደሚሉት የኢትዮጵያ ብሄራዊ የወንዶች ቡድን አጥቂውን ፍቅሩ ተፈራን በቡድኑ እንዲያካትትና ሌሎች ውጪ አገር የሚገኙ ተጨዋቾች ካሉ እንዲያፈላልግ መክረዋል።ከቅዱስ ጊዮርጊስን በቃኝ ብሎ ወደ ደቡብ አፍሪካ በመሄዱ ጥርስ የተነከሰበት ፍቅሩ ጥሪ ከተደረገለት አገሩን ለማገልገል ሙሉ ፈቃደኛ መሆኑን ለህዝብና ለሚመለከታቸው አካላት አስታውቋል። በአሁኑ ወቅት ቪየትናም ለታዋቂ ክለብ በአጥቂ ስፍራ በመጫወት ጎል እያመረተ ያለው ፍቅሩ ተፈራ አሁን በብሄራዊ ቡድኑ ውስጥ ከታቀፉት የተሻለ እንደሆነ ስለወቅታዊ ብቃቱ የሚያውቁና፣ በዩቲዩብ የሚታየው እንቅስቃሴው ይመሰክራል። ፍቅሩ ተፈራ ባለሃብቱ ሼኽ መሃመድ አላሙዲ የሚደጉሙትና አቶ አብነት የሚመሩት ቅ/ጊዮርጊስን ጥሎ መሄዱና ፌዴሬሽኑን በኩዴታ ተረክበው የሚቆጣጠሩት እነዚሁ ክፍሎች በመሆናቸው ሳቢያ እንዳልተመረጠ እየተጠቆመ ነው።
ብ/ጄኔራል ሞላ ከሃላፊነታቸው ተነሱ 
የአየር ሃይል አዛዥ ሜ/ጄኔራል ሞላ ሀ/ማርያም ከሃላፊነታቸው መነሳታቸውን የኢሳት ሬዲዮ አስታውቋል። የበረራ መምህርና የጦር ጀት አብራሪ የነበሩት ካፒቴን ተሾመ ተንኮሉ ከተረጋገጠ ምንጭ መስማታቸውን በመግለጽ “ወዲ ዘውዴ” በመባል የሚታወቁት የመለስና የመከላከያ የኤታማጆር ሹም ሳሞራ የኑስ ወዳጅ የተባሉት ሜ/ጄኔራል መሃሪ ዘውዴ ተክተዋቸዋል።
ኢየሩሳሌም አርአያ በመባል የሚታወቁት ጸሀፊ በተለያዩ ድረገጾች ባሰራጩት ዘገባ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት ታላቅ ገድል የፈጸሙ ከፍተኛ የጦር መኮንን እንደሆኑ የሚያውቋቸው መመስከራቸውን ጠቅሰዋል። ኢየሩሳሌም አርአያ እንዳሉት ሜ/ጄኔራል ሞላ መለስንና ሳሞራን ይቃወሙ ነበር። በተለይም አሰብን ለመያዝ በተሰራ ኦፕሬሽን መበላሸትና ባድመን መልሶ ለኤርትራ ለመስጠት በተዘጋጀው ባለ አምስት “የክህደት” አጀንዳ ላይ ተቃውሞ ያሰሙ መኮንን ናቸው ብለዋል።
በዚሁ ጽሁፍ ላይ ሜ/ጄኔራል ሞላ በአቋማቸው በመጽናታቸው የአንጃው ደጋፊ በሚል ቀደም ብሎ ጥርስ የተነከሳባቸው መኮንን እንደነበሩ ያስረዳል። በማያያዝም አየር ሃይልን እንዲመሩ የተሾሙት ወዲ ዘውዴ የኤርትራ ደም ያላቸው፣ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት ፈሪ ተብለው የተገመገሙ የጦር መኮንን መሆናቸውን ገልጸዋል። ወዲ ዘውዴ በቅርቡ የሜ/ጄ ማዕረግ ከተሰጣቸው ሶስት ጄኔራሎች መካከል አንዱ እንደሆኑ ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment