Translate

Monday, February 18, 2013

ቴዲ አፍሮ በስራው ተከብሮ ተሸለመ


(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)

teddy awarded


ቴዲ አፍሮ በስራው ተከብሮ ተሸለመ
ታዋቂ የሚባሉት የኪነት ባለሙያዎች በአብዛኛው የህዝብ አንደበት ከመሆን ይልቅ “አጫፋሪነትን” መርጠዋል በሚል በሚዘለፉበት ወቅት ላይ ከየአቅጣጫው ምስጋና፣ ውዳሴና አድንቆት የሚዘንብበት ቴዲ አፍሮ በስራው ተከብሮ ተሸለመ።

በካሊፎርኒያ ግዛት የሳን ሆዜ ከተማ (City of San Jose) በኢትዮጵያና በኤርትራ ወዳጆች ፎረም ስም ቴዲ አፍሮን የሸለመው ፌብሩዋሪ 15 ቀን 2013 ነው። የምስጋና ሽልማት /Commendation Award/ የተሰጠው ቴዲ አፍሮ ስለተሰጠው ሽልማት የቀረበው ምክንያት “ራሱን ለሰላምና ለመፈቃቀር አግልግሎት አሳልፎ ሰተ በጣም ተደናቂና ታዋቀቂ የሙዚቃ ሰው” በሚል ሙገሳ መሆኑን የቴዲ አፍሮ የፌስቡክ ገጽ ጠቁሞዋል።
ቴዲ አፍሮ በኤርትራ አዲስ ትውልድ ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት ያለው የጥበብ ሰው ነው። አርቆ በማስተዋልና ጊዜና ወቅት ጠብቆ አነጋጋሪ ስራ በማቅረብ ለጥበቡ የተፈጠረ ሰው መሆኑንን በተደጋጋሚ አሳየው ቴዲ በፑንት ላንድ ሞት ሊፈረድበት የነበረውን የትግራይ ተወላጅ ከመንግስት ቀድሞ በመቶ ሺዎች በመክፈል ነፍስ ያተረፈ የዘመኑ ድንቅ ሰው ነው። ቴዲ አስተዋዩን መሪ አጤ ሚኒልክን ከተኙበት ቀስቅሶ ታሪካቸውን በማደስም በኩል የሰራው ስራ “ጥቁር ሰው” የሚለውን አሻራ ለተተኪው ትውልድ እንዲቀመጥለት አድርጓል።
ደደቢቶች ዳክዬ አንበላም አሉ
(ፎቶ: ethiofootball.com)
የደደቢት እግር ኳስ ቡድን ዛሬ የመጀመሪያውን ጨዋታ ለማከናወን ወደ መካከለኛዋ አፍሪካ ያቀናው በካሜሮን በኩል ነው፡፡ ገነነ መኩሪያን (ሊብሮ) በመጥቀስ የሃበሻ ዶት ኮም እንደደዘገበው ‹‹ሙቀቱ 36 ዲግሪ ነው፡፡ ምግብ ችግር አለ። ሩዝ ነው የሚሰጡን፣ ፓስታ እንኳን የላቸውም፡፡ ስጋ የሚባል አይታሰብም፡፡ ራት ላይ የዶሮ ስጋ ብለው ሊያቀርቡልን ነበር። ስናጣራ የዳክዬ ነው፡፡ ከባህላችን አንፃር ዳክዬ መብላቱ አልተፈለገም ሩዙን እየታገልነው ነው፡፡ መኝታም ችግር ነው፡፡ ምንም የተመቻቸ ነገር የለም፡፡ ከተማው አዋራ ነው። ስታዲየሙ ግን ምርጥ ነው” በማለት ተጨዋቾቹ መናገራቸውን አስነብቧል፡፡ ተጨዋቾቹ እንዳሉት ኤሮፖርት ችግር ነበር፡፡ ፖሊሶች ፓስፖርታቸውን በመያዝ አብረዋቸው የተጓዙትን ጋዜጠኞችንም ጭምር አጉላልተዋል፡፡ ለያንዳዳቸው 45 ዶላር እየተከፈለ ነው ፓስፖርቱ የተሰጣቸው፡፡
ድርጊቱ በትክክል ከተፈጸመ በካፍ ህግ መሰረት ያስቀጣል። በዘገባው ላይ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የተፈጠረውን ችግር አስመልክቶ ስላደረገው እንቅስቃሴ የተባለ ነገር የለም። ተረበኞች ደደቢት ከሰራዊቱ አባላት አንድ አስር የሚሆኑትን ትጥቅ አስለብሶና የአቶ መለስን ፎቶ አስቀድሞ አውሮፕላን ማረፊያ ቢያሳይ ኖሮ ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋ ይሆንላቸው ነበር ብለዋል። በነገራችን ላይ ብሔራዊ ቡድን እድገት የሚለካው በክለቦች ውጤት ነውና ሰበብ ማብዛቱ ዋጋ የለውም።
ፖሊስ ኤርሚያስ አመልጋን ለቀቀ
በኢኮኖሚ ጉዳዮች ቀዳሚ አስተያየት በመስጠት የሚታወቁት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ከደረቅ ቼክ ጋር በተያያዘ ፖሊስ በቁጥጥር ስር እንዳዋላቸው ፎርቹን ቅዳሜ አስነብቦ ነበር። አቶ ኤርሚያስ መታሰራቸውን የገለጸው ፎርቹን በተመሳሳይ ቀን መለቀቃቸውን ቢዘግብም ዝርዝር ጉዳዩን አላወሳም ነበር።
እሁድ ለንባብ የበቃው ሪፖርተር አቶ ኤርሚያስ መፈታታቸውንና እሳቸው ያቋቋሙት አክሰስ ሪል ስቴት ምርመራው እንደተቋረጠ መግለጹን አመልክቷል። ተጠርጣሪው አቶ ኤርሚያስ የደረቅ ቼክ መዘዝን ጠንቅቀው የሚያውቁና በእንዲህ ያለ ተራ ተግባር ይሳተፋሉ ተብሎ ስለማይገመት ወሬው በከፍተኛ ደረጃ ተሰራጭቶና የዘመን ባንክና የአክሰስ ሪል ስቴት ደንበኞችን አስደንግጦ ነበር።
ካሳንቺስ ስድስተኛ ፖሊስ ጣቢያ አንድ ቀን ያደሩት አቶ ኤርሚያስ የተጠረጠሩበት ምክንያት የአክሰስ ሪል ስቴት ኩባንያ አንድ ደንበኛ ኩባንያው እሠራለሁ ያለውን ቤት ሠርቶ በወቅቱ አላስረከበኝም በማለት ገንዘባቸው እንዲመለስ ሲጠይቁ፣ የ350 ሺሕ ብር ቼክ ፈርመው ከሰጡ በኋላ ቼኩን የተቀበሉት ሰው የጠየቁት ገንዘብ በባንክ ሂሳቡ ውስጥ አለመኖሩ ሲነገራቸው ለፖሊስ ክስ በማቅረባቸው ነው።
ምንጮች እንደሚገልጹት በማለት ሪፖርተር ጥብቅና የቆመ በሚያስመስለው ዜናው አካውንቱ ውስጥ ገንዘብ እንደነበር ማረጋገጡን፣ ነገር ግን ሌላ የሪል ስቴቱ ደንበኛ አካውንቱን በፍርድ ቤት በማሳገዳቸው ገንዘቡን ማንቀሳቀስ አንዳልተቻለ፣ አክሰስ ካሉት አካውንቶች ውስጥ በአንደኛው ከ1.7 ሚሊዮን ብር በላይ እንደነበር ሪፖርተር መረዳት ችሏል፡፡ ይህም መረጃ ለመርማሪዎቹ ቀርቦ የይከፈለኝ ጥያቄ ላነሱት ግለሰብ ገንዘቡ ተከፍሏቸዋል፡፡ ግለሰቡም ወዲያው ክሱን በማንሳታቸው ምርመራው ተቋርጦ አቶ ኤርሚያስም ተለቀዋል፡፡ አክሰስ ሪል ስቴት ለሪፖርተር በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ በአካውንቱ ውስጥ በቂ ገንዘብ መኖሩን አረጋግጧል፡፡ የተፈጠረው ክስተትም በቢዝነስ እንቅስቃሴ ውስጥ በየጊዜው የሚያጋጥም መሆኑን የገለጸው አክሰስ፣ መርማሪዎቹ ይህንኑ ተረድተው ምርመራውን ማቋረጣቸውን አስታውቋል፡፡
አቶ ኤርሚያስ የሰጡት ቼክ ራሳቸው ካቋቋሙት ዘመን ባንክ በመሆኑ፣ ሌላ ተበዳይ አካውንቱን አስቀድመው ማሳገዳቸውና እግዱ ከፖሊስ ምርመራና እስር በኋላ መሆኑ ጥርጣሬ የፈጠረባቸው ክፍሎች ድርጊቱ ቢዝነሳቸው ላይ አደጋ ሊፈጥር እንደሚችል ግምታቸውን ሰጥተዋል።
“መንግስት” የኤሌክትሪክ ሃይል እጥረት ይከሰታል አለ
ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ልማትን ለማፋጠን እያደረገች ባለው ጥረትና በሌሎች ኢኮኖሚያዊ ክስተቶች የተነሳ በቀጣዩ ዓመት ቢያንስ እስከ 200 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል እጥረት እንደሚከሰት ሪፖርተር ከመንግስት ያገኘውን ማስረጃ በማጣቀስ አስታወቀ።
ሒላሪ ክሊንተን በአዲስአበባ ለአፍሪካ መሪዎች "በሻማ" ንግግር ሲያደርጉ
ለጅቡቲ ኤሌክትሪክ በመሸጥ ላይ የሚገኘው መንግስት ይከሰታል ያለውን እጥረት ችግር ከመፍጠሩ በፊት ከወዲሁ ዝግጅት ለማድረግ የመረጠው የጂኦተርማል /የእንፋሎት/ ሃይልን መጠቀም ነው። እየተሰሩ ያሉት አዳዲስ የሃይል ማመንጫዎች በሚቀጥለው ዓመት ስለማይጠናቀቁ ፊቱን ወደ ጂኦተርማል ሃይል ግንባታ ያዞረው መንግስት ብድር እንደሚያፈላልግም ሪፖርተር አመልክቷል።
በመሆኑም እጥረቱን ለመቅረፍ በሌላ ወጪና ጊዜ ቆጣቢ አማራጭ ላይ መተኮር እንዳለበት በመንግሥት የተቀመጠው ውሳኔ ያመለክታል፡፡ በአማራጭነት ከተወሰዱት በፍጥነት ሊደርሱ ከሚችሉ መፍትሔዎች መካከል የጂኦተርማል (እንፋሎት) ኤሌክትሪክ ኃይል ሲሆን፣ በዚህም ሥራ ላይ የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ጋር በጋራ በመሥራት ችግሩን የመቅረፍ ኃላፊነት እንደተሰጠው የሪፖርትር ዜና ያስረዳል።
የሃይል እጥረትና መቋረጥ እንግዳ ላልሆነበት ህዝብ አስቀድሞ ይህንን መሰሉ መግለጫ መስጠት ትርጉም ዓልባ እንደሆነ የሚጠቁሙት የሕዝብ አስተያየቶች በአምስቱ ዓመት የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ኢህአዴግ ከኢትዮጵያውያን ይልቅ ጎረቤት አገሮች በኃይል አቅርቦት ራሳቸውን እንዲችሉ ማድረጉ የዕቅዱ ከጅምሩ መሳካት አመላካች ነው በማለት የኢህአዴግን ‹‹የጽድቅ›› ሥራ ‹‹ያወድሳሉ››፡፡ ሥልጣን በተቆጣጠሩ ወቅት በቀጣይ 10ዓመታት ለኢትዮጵያ ያላቸው ህልም ምን እንደሆነ ተጠይቀው ህዝቡን በቀን ሦስት ጊዜ መመገብ እንደሆነ የተናገሩት ‹‹ባለራዕዩ›› መሪ ግልገል ጊቤ በተመረቀ ሰሞን ሻማ በኤሌክትሪክ መቋረጥ ለሚከሰት ችግር ሳይሆን ለልደት ብቻ እንደሚበራ በመግለጽ ‹‹ውርሳቸውን (ሌጋሲያቸውን)›› ትተው አልፈዋል፡፡
የአማራ ጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ተነክሯል
ሙስናን ለመቆጣጠር የተቋቋመው የአማራ ክልል የጸረ ሙስና ኮሚሽን ራሱ በሙስና ውስጥ ተነክሮ መገኘቱን ኢሳት የካቲት 8 ቀን 2005 ባሰራጨው ዜና አስታወቀ። የክልሉን ሰራተኞችና የኢህአዴግ አባላት በምንጭነት ጠቅሶ ኢሳት እንደገለጸው የክልሉ ባለስልጣናት ከባለሀብቶች ጋር በመመሳጠር በባህርዳር ከተማ ከፍተኛ የመሬት ችብቸባ ማካሄዳቸው የሚታወቅ ቢሆንም፣ የክልሉ የጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ተዋናይ በመሆኑ አደጋውን ለመከላከል አንዳልቻለም።
(ፎቶ: skyscrapercity.com)
አራት ተጠርጣሪዎች በክልሉ ጸረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ አማካይነት ክስ ተመስርቶባቸው በቁጥጥር ስር ውለው ፍርድ ቤት ቀርበው ነበር። ዳኛው ክሱ ዋስ ያሰጣል አያሰጥም በሚለው ውሳኔ ለመስጠት ቀጠሮ ከተሰጠና ተጠርጣሪዎቹ ወደ እስር ቤት ከተመለሱ በኋላ የጸረ ሙስና ኮሚሽነሩ ተጠርጣሪዎቹ የዋስ መብታቸው እንዲከበር የሚጠይቅ ደብዳቤ ለፍርድ ቤት መላካቸውን ኢሳት ዘግቧል። በዚሁ መሰረት ችሎቱ በድጋሚ ተሰይሞ እያንዳንዳቸው በ5ሺህ በር ዋስ እንቢለቀቁ ተደርጓል። በስፍራው የነበሩ አንድ ባለሀብት ለሁሉም ተከሳሾች የዋስትና ገንዘብ በማስያዝ እንዲለቀቁ አድርገዋል።
ሰራተኞቹ እንደገለጡት የጸረ ሙስና ኮሚሽን ባለስልጣናት እስረኞችን በዋስ ለማስለቀቅ 30 ሺ ብር፣ ክሱን ለመሰረዝ ደግሞ 150 ሺ ብር ለመቀበል ከባለሀብቶች ጋር ተደራድረዋል። በከፍተኛ ሙስና የተከሰሱት ሰራተኞች ላለፉት ሶስት ወራት አንድም ቀን ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀድሞ በነበራቸው የሀላፊነት ቦታዎች ላይ እየሰሩ እንደሚገኙ ታውቋል። አብዛኛውን ውሎውን በመስሪያ ቤቱ አድርጎ የነበረው የኮሚሽኑ ባለስልጣንም ምርመራውን ማቋረጡ ታውቋል ሲል ኢሳት ዘገባውን ይቋጫል። ኢሳት የክልሉን የጸረ ሙስና ኮሚሽን ለማነጋገር ያደረገው ሙከራ እንዳልተሳካለትም አመልክቷል።
የኢሳት የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም በኖርዌይ
በኖርዌይ ለኢሳት የተደረገ የገንዘብ መዋጮ ስብሰባ ዝግጅት በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን ሄለን ዘውዱ አየለ የሚባሉ የጎልጉል ድረገጽ ጋዜጣ ተከታታይ በላኩት የኢሜል መልዕክት አስታውቀዋል፡፡ በስብሰባ ላይ ንግግር ማድረጋቸውን የገለጹት ሄለን ዘውዱ አየለ “አለም ወደ አንድ መንደር በመጣችበት በዚህ ዘመን መንግስት አልባዋ ሱማሌ እንኳን በነጻነት በግል የሚንቀሳቀሱ የተለያዩ የራዲዮ እና የቲቪ ጣቢያዎች ባለቤት ናት። መገናኛ ብዙሃን የአንድ ሃገር የዲሞክራሲ ደረጃ ብቻ ሳይሆን የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ ዕድገትም መሰረት ነው፤ በቅርቡ ዘ ኢኮኖሚስት የተባለው ዓለም አቀፍ ወርሃዊ መጽሄት እንደዘገበው የስካንዲኒቪያ ሃገሮች ከሌሎች የበለጸጉ ሃገሮች ልቀው የሚገኙት በሚዲያ እና ኮሚኒኬሽን ዕድገታቸው ነው ብሎ ዘግቦአል። ስለዚህም የፖለቲካ ትግላችን የሚዲያ ግንባር ቀደምተነት ያገናዘበ መሆን ይገባዋል” በማለት መናገራቸውን በላኩልን መልዕክታቸው ላይ ጠቅሰዋል፡፡
ከንግግራቸው በተጨማሪም የገንዘብ ስብሰባውን አስመልክቶ የራሣቸውን ምልከታ እንደሚከተለው ልከውልናል፤
‹‹የኖርዌይ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ዕሑድ የካቲት 10 ቀን 2013 በደመቀ ሁኔታ ተከብሯል። አዳራሹን ሞልተው በጉጉት የጠበቁት በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም ተወዳጁ የኪነ ጥበብ ሰው ታማኝ በየነ ወደ አዳራሹ ሲገባ በጋለ ስሜት ደማቅ አቀባበል አድርገውለታል። የተለያዩ የእንኳን ደህና መጣህ ንግግሮች ተደርገዋል።
‹‹ተወዳጁ የኪነ ጥበብ ሰው ታማኝ በየነ በሃገርና በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለው የመብት ረገጣ አስመልክቶ በመረጃ የተደገፉ ትንታኔዎችን አቅርቧል። ልምዱንም አካፍሏል። በቀጣይ የጥበብ ሰው አርቲስት ታማኝ በየነ ወደ ዋናው የገቢ ማሰባሰቢያ የጨረታ መርሃ ግብር ተሸጋገረ። ለጨረታ የቀረበው የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ነበር ።ጨረታውን ለማሸነፍ የነበረው ፉክክር የአገር ፍቅር ሰሜት የተንጸባረቀበት ሲሆን፣ በዚሁ ታላቅ ታሪካዊ ባዋጋው ከፍተኛ በሆነበት ጨረታ አሸናፊው የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ በክብር ተረክበውታል።
‹‹በአርቲስት እንዳለ እና በወጣቶች የተዘጋጀ የምርጫ 97 ድምፃችን ይመለስ በሚል ሰላማዊ ሰልፍ ወጥተው የተገደሉ ወጣት ሰላሚዊ ሰልፈኞችን ሁኔታ ያስታወስ ታሪካዊ ድራማ እና በየዝግጅቱ ጣልቃ አዝናኝ ሙዚቃዎች ቀርቦአል።››
ለኢሣት የተደረገውን የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም አስመልክቶ ኢሣትን ጨምሮ በርካታ ሚዲያዎች ዘግበውታል፡፡ ከተመሠረተ ከሚያዚያ 16፤2002ዓም (April 24, 2010) ጀምሮ ፕሮግራሞቹን ለኢትዮጵያ ሕዝብ እንዳያደርስ ተደጋጋሚ የስርጭት አፈናና ሽበባ ከህወሃት/ኢህአዴግ እየደረሰበት እንደሆነ የሚገለጸው ኢሣት ዕለታዊ ፕሮግራሞቹን ላለፉት ሦስት ዓመታት ያህል በዩ ትዩብ (You Tube) ለህዝብ እንዲደርስ እያደረገ ይገኛል፡፡
አዜብ መስፍን፤ ከወልቃይት እስከ ቂርቆስ
(ፎቶ: ምንጩ ያልታወቀ)
የትውልድ ቦታቸውና የመጨረሻ ማረፊያቸው እያወዛገበ ያለው ወ/ሮ አዜብ መስፍን የአዲስ አበባ አስተዳደርን ለመምራት ቂርቆስ ክፍለ ከተማ የኢህአዴግ ወዳጅ ከሆነው ኢዴፓ ጋር ሊፈታተኑ እንደሆነ ተሰምቷል፡፡ የሳምንቱ መነጋገሪያ የሆነው የወ/ሮ አዜብ የአዲስ አበባ እጩ ተወዳዳሪ ሆኖ መቅረብ የቂርቆስ ሕዝብ የሚፈተንበት እንደሆነ ተገምቷል፡፡ የአዲስ አበባን ምርጫ ብቻውን ደግሶ ብቻውን ለመመገብ ቀን እየቆጠረ ያለው ኢህአዴግ ወ/ሮ አዜብን አንዲፎካከሩ ያስቀመጠላቸው አቶ ወንደሰን ተሾመን እንደሆነ የገለጸው ሪፖርተር ነው፡፡
የወልቃይት ጠገዴን ሕዝብ አስከፍተዋል በሚል የሚወቀሱት ወ/ሮ አዜብ በአዲስ አበባ አስተዳደር ተመራጭ ከሆኑ አምስት ዓመት በሥልጣን ስለሚቆዩ ለዳግም ምርጫ ወልቃይትን በፓርላማ ለመወከል ወደትግራይ እንደማይሄዱ ተገምቷል፡፡ ይህም የሆነው ‹‹ባለራዕዩ›› ባለቤታቸው ካለፉ በኋላ ከትግራይ ተገፍተው ወዳስከፉት ወልቃይት በመጠጋጋታቸው ነው፡፡ ወ/ሮ አዜብ ተመልሰው ባስከፉት ሕዝብ ለፓርላማ ሊመረጡ ስለማይችሉ ያሁኑ አካሄዳቸው አዲስ አበባ የማስተዳደሩን ኃላፊነት በቂርቆስ ሕዝብ ስም ለመረከብ የታለመ ይመስላል፡፡
አዜብ መስፍን የባለቤታቸው ‹‹ውርስ (ሌጋሲ)›› እስካልተበረዘ ድረስ ተግባራዊ ለማድረግ ቃል መግባታቸው የሚታወስ ሲሆን በዚያው ንግግራቸው ወቅት ‹‹ቀሪውን ጊዜ ልጆቼን በማሳደግ እፈተናለሁ›› ማለታቸው አይዘነጋም፡፡

No comments:

Post a Comment